ምዕራፍ 96

ከምርኮ በኋላ ቤት በተሠራ ጊዜ።

ለእግዚአብሔር አዲስ ምስጋናን አመስግኑ፤ ምድር ሁሉ፥ እግዚአብሔርን አመስግኑ።
2 እግዚአብሔርን አመስግኑ ስሙንም ባርኩ፥ ዕለት ዕለትም ማዳኑን አውሩ።
3 ክብሩን ለአሕዛብ ተኣምራቱንም ለወገኖች ሁሉ ንገሩ፤
4 እግዚአብሔር ታላቅ ምስጋናውም ብዙ ነውና፥ በአማልክትም ሁሉ ላይ የተፈራ ነውና።
5 የአሕዛብ አማልክት ሁሉ አጋንንት ናቸውና፤ እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ሠራ።
6 ምስጋናና ውበት በፊቱ፥ ቅዱስነትና ግርማ በመቅደሱ ውስጥ ናቸው።
7 የአሕዛብ ወገኖች፥ ለእግዚአብሔር አምጡ፥ ክብርና ምስጋናን ለእግዚአብሔር አምጡ፤
8 ለስሙ የሚገባ ክብርን ለእግዚአብሔር አምጡ፤ ቍርባን ያዙ ወደ አደባባዮችም ግቡ።
9 በቅድስናው ስፍራ ለእግዚአብሔር ስገዱ፤ ምድር ሁሉ በፊቱ ትነዋወጥ።
10 በአሕዛብ መካከል። እግዚአብሔር ነገሠ በሉ። እንዳይናወጥም ዓለሙን እርሱ አጸናው፥ አሕዛብንም በቅንነት ይፈርዳል።
11 ሰማያት ደስ ይበላቸው፥ ምድርም ሐሤትን ታድርግ፤ ባሕርና ሞላዋ ይናወጡ፤
12 በረሃ በእርስዋም ያሉ ሁሉ ሐሤትን ያድርጉ፤ የዱር ዛፎች ሁሉ በዚያን ጊዜ በእግዚአብሔር ፊት ደስ ይላቸዋል፤
13 ይመጣልና፤ በምድር ላይ ሊፈርድ ይመጣልና፤ እርሱም ዓለምን በጽድቅ አሕዛብንም በቅንነት ይፈርዳል።