ምዕራፍ 112

ሃሌ ሉያ። እግዚአብሔርን የሚፈራ፥ ትእዛዙንም እጅግ የሚወድድ ሰው ምስጉን ነው።
2 ዘሩ በምድር ላይ ኃያል ይሆናል፤ የቅኖች ትውልድ ትባረካለች።
3 ክብርና ባለጠግነት በቤቱ ነው፥ ጽድቁም ለዘላለም ይኖራል።
4 ለቅኖች ብርሃን በጨለማ ወጣ፤ መሓሪና ይቅር ባይ ጻድቅም ነው።
5 ቸር ሰው ይራራል ያበድራልም፥ በፍርድም ነገሩን ይፈጽማል።
6 ለዘላለም አይናወጥም፤ የጻድቅ መታሰቢያ ለዘላለም ይኖራል።
7 ከክፉ ነገር አይፈራም፤ በእግዚአብሔር ለመታመን ልቡ የጸና ነው።
8 በጠላቶቹ ላይ እስኪያይ ድረስ ልቡ ጽኑ ነው፥ አይፈራም።
9 በተነ ለችግረኞችም ሰጠ፤ ጽድቁ ለዘላለም ዓለም ይኖራል፤ ቀንዱ በክብር ከፍ ከፍ ይላል።
10 ኃጢአተኛም አይቶ ይቈጣል፥ ጥርሱንም ያፋጫል፥ ይቀልጣልም፤ የኃጢአተኞችም ምኞት ትጠፋለች።