ምዕራፍ 35

የዳዊት መዝሙር።
አቤቱ፥ የሚበድሉኝን በድላቸው፥ የሚዋጉኝንም ተዋጋቸው።
2 ጥሩርና ጋሻ ያዝ፥ እኔንም ለመርዳት ተነሥ።
3 ሰይፍህን ምዘዝ የሚያሳድዱኝንም መንገዳቸውን ዝጋ፤ ነፍሴን። መድኃኒትሽ እኔ ነኝ በላት።
4 ነፍሴን የሚሹ ሁሉ ይፈሩ ይጐስቈሉም፤ ክፉትን በእኔ ላይ የሚያስቡ ይፈሩ ወደ ኋላቸውም ይበሉ።
5 በነፋስ ፊት እንዳለ ትቢያ ይሁኑ፥ የእግዚአብሔርንም መልአክ ያስጨንቃቸው።
6 መንገዳቸው ዳጥና ጨለማ ይሁን፥ የእግዚአብሔርም መልአክ ያሳድዳቸው።
7 በከንቱ ያጠፉኝ ዘንድ ወጥመዳቸውን ሸሽገውብኛልና፥ ነፍሴን በከንቱ አበሳጭተዋልና።
8 ያላወቁት ወጥመድ ይምጣባቸው፥ የሸሸጉትም ወጥመድ ይያዛቸው፤ በዚህ ወጥመድ ውስጥ ይውደቁ።
9 ነፍሴ ግን በእግዚአብሔር ደስ ይላታል፥ በማዳኑም ሐሴት ታደርጋለች።
10 አጥንቶቼ ሁሉ እንዲህ ይሉሃል። አቤቱ፥ እንደ አንተ ማን ነው? ችግረኛን ከሚቀማው እጅ፥ ችግረኛንና ድሀውንም ከሚነጥቀው እጅ ታድነዋለህ።
11 የክፋት ምስክሮች ተነሡብኝ፥ የማላውቀውንም በእኔ ላይ ተናገሩ።
12 ስለ በጎ ክፋትን መለሱልኝ፥ ነፍሴንም ልጆችን አሳጡአት።
13 እኔስ እነርሱ በታመሙ ጊዜ ማቅ ለበስሁ፥ ነፍሴንም በጾም አደከምኋት፤ ጸሎቴም ወደ ብብቴ ተመለሰ።
14 ለወዳጄና ለወንድሜ እንደማደርግ አደረግሁ፤ ለእናቱም እንደሚያለቅስ ራሴን ዝቅ ዝቅ አደረግሁ።
15 በእኔ ላይ ተሰበሰቡ ደስም አላቸው፤ ግፈኞች በእኔ ላይ ተሰበሰቡ እኔም አላውቅሁም፤ ቀደዱኝ አልተውኝምም።
16 ፈተኑኝ በሣቅም ዘበቱብኝ፥ ጥርሳቸውንም በእኔ ላይ አንቀጫቅጩ።
17 አቤቱ፥ እስከ መቼ ድረስ ታይልኛለህ? ነፍሴን ከክፉ ሥራቸው ብችነቴንም ከአንበሶች አድናት።
18 አቤቱ፥ በታላቁ ጉባኤ ውስጥ እገዛልሃለሁ፥ በብዙ ሕዝብ መካከልም አመሰግንሃለሁ።
19 በግፍ የሚጠሉኝ በላዬ ደስ አይበላቸው፥ በከንቱ የሚጣሉኝም በዓይናቸው አይጣቀሱብኝ።
20 ለእኔስ ሰላምን ይናገሩኛልና፥ በቍጣም ሽንገላን ይመክራሉ።
21 አፋቸውንም በእኔ ላይ አላቀቁ፤ እሰይ እሰይ፥ ዓይናችን አየው ይላሉ።
22 አቤቱ፥ አንተ አየኸው፤ ዝም አትበል፤ አቤቱ፥ ከእኔ አትራቅ።
23 አምላኬ ጌታዬም፥ ወደ ፍርዴ ተነሥ፥ አቤቱ፥ ፍርዴን አድምጥ።
24 አቤቱ አምላኬ፥ እንደ ጽድቅህ ፍረድልኝ፥ በላዬም ደስ አይበላቸው።
25 በልባቸው። እሰይ እሰይ፥ ነፍሳችንን ደስ አላት አይበሉ፤ ደግሞም። ዋጥነው አይበሉ።
26 በመከራዬ ደስ የሚላቸው ይፈሩ፥ በአንድነትም ይጐስቍሉ፤ በእኔ ላይ የሚታበዩ እፍረትንና ጕስቍልናን ይልበሱ።
27 ጽድቄን የሚወድዱአት ደስ ይበላቸው ሐሴትንም ያድርጉ፤ የባሪያውን ሰላም የሚወድድ እግዚአብሔር ታላቅ ይሁን ዘወትር ይበሉ።
28 ምላሴ ጽድቅህን ሁልጊዜም ምስጋናህን ይናገራል።