ምዕራፍ 62

ለመዘምራን አለቃ፤ ስለ ኤዶታም፤ የዳዊት መዝሙር።

ነፍሴ ለእግዚአብሔር የምትገዛ አይደለችምን? መድኃኒቴ ከእርሱ ዘንድ ናትና።
2 እርሱ አምላኬ መድኃኒቴም ነውና፤ እርሱ መጠጊያዬ ነው፥ እጅግም አልታወክም።
3 እስከ መቼ በሰው ላይ ትቆማላችሁ? እናንተ ሁላችሁ እንዳዘነበለ ግድግዳ እንደ ፈረሰም ቅጥር ትገድላላችሁ።
4 ነገር ግን ክብሬን ይሽሩ ዘንድ መከሩ፥ ሐሰትንም ይወድዳሉ፤ በአፋቸው ይባርካሉ፥ በልባቸውም ይረግማሉ።
5 ነገር ግን፥ ነፍሴ ሆይ፥ አንቺ ለእግዚአብሔር ተገዢ፥ ተስፋዬ ከእርሱ ዘንድ ናትና።
6 እርሱ አምላኬ መድኃኒቴም ነውና፤ እርሱ መጠጊያዬ ነው፤ አልታወክም።
7 መድኃኒቴና ክብሬ በእግዚአብሔር ነው፤ የረድኤቴ አምላክ ተስፋዬም እግዚአብሔር ነው።
8 የሕዝብ ማኅበር ሁላችሁ፥ በእርሱ ታመኑ፥ ልባችሁንም በፊቱ አፍስሱ፤ እግዚአብሔር ረዳታችን ነው።
9 ነገር ግን የሰው ልጆች ከንቱ ናቸው፥ የሰው ልጆችም ሐሰተኞች ናቸው፤ በሚዛንም ይበድላሉ፥ እነርሱስ በፍጹም ከንቱ ናቸው።
10 ዓመፃን ተስፋ አታድርጉ፥ ቅሚያንም አትተማመኑት፤ ባለጠግነት ቢበዛ ልባችሁ አይኵራ።
11 እግዚአብሔር አንድ ጊዜ ተናገረ፥ እኔም ይህን ብቻ ሰማሁ፤ ኃይል የእግዚአብሔር ነው፥
12 አቤቱ፥ ምሕረትም ያንተ ነው፤ አንተ ለእያንዳንዱ እንደ ሥራው ፍዳውን ትሰጣለህና።