ምዕራፍ 40

ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።

ቆይቼ እግዚአብሔር ደጅ ጠናሁት፥ እርሱም ዘንበል አለልኝ ጩኽቴንም ሰማኝ።
2 ከጥፋት ጕድጓድ ከረግረግም ጭቃ አወጣኝ፥ እግሮቼንም በድንጋይ ላይ አቆማቸው፥ አረማመዴንም አጸና።
3 አዲስ ዝማሬን ለአምላካችን ምስጋና በአፌ ጨመረ፤ ብዙዎች ያያሉ ይፈሩማል፥ በእግዚአብሔርም ይታመናሉ።
4 እግዚአብሔርን የታመነ ወደ ትዕቢተኛና ወደ ሐሰተኛ ያልተመለከተ ሰው ምስጉን ነው።
5 አቤቱ አምላኬ፥ ያደረግኸው ተአምራት ብዙ ነው፥ አሳብህንም ምንም የሚመስለው የለም፤ ባወራም ብናገርም ከቍጥር ሁሉ በዛ።
6 መሥዋዕትንና ቍርባንን አልወደድህም፤ ሥጋን አዘጋጀህልኝ፤ የሚቃጠለውንና ስለ ኃጢአት የሚቀርበውን መሥዋዕት አልሻህም።
7 በዚያን ጊዜ አልሁ። እነሆ፥ መጣሁ፤ ስለ እኔ በመጽሐፍ ራስ ተጽፎአል፤
8 አምላኬ ሆይ፥ ፈቃድህን ለማድረግ ወደድሁ፥ ሕግህም በልቤ ውስጥ ነው።
9 በታላቅ ጉባኤ ጽድቅን አወራሁ፤ እነሆ፥ ከንፈሮቼን አልከለክልም፤ አቤቱ፥ አንተ ጽድቄን ታውቃለህ።
10 እውነትህንም በልቤ ውስጥ አልሰወርሁም፥ ማዳንህንም ተናገርሁ፤ ምሕረትህንና እውነትህን ከታላቅ ጉባኤ አልሰወርሁም።
11 አቤቱ፥ አንተ ምሕረትህን ከእኔ አታርቅ፤ ቸርነትህና እውነትህ ዘወትር ይጠብቁኝ።
12 ቍጥር የሌላት ክፋት አግኝታኛለችና፤ ኃጢአቶቼ ያዙኝ፥ ማየትም ተስኖኛል ከራሴ ጠጕር ይልቅ በዙ፥ ልቤም ተወኝ።
13 አቤቱ፥ ታድነኝ ዘንድ ፍቀድ፤ አቤቱ፥ እኔን ለመርዳት ፍጠን።
14 ነፍሴን ለማጥፋት የሚወድዱ ይፈሩ፥ በአንድነትም ይጐስቍሉ፤ በእኔ ላይ ክፋትን ሊያደርጉ የሚወድዱ ወደ ኋላቸው ይመለሱ ይጐስቍሉም።
15 እሰይ እሰይ የሚሉኝ እፍረታቸውን ወዲያው ይከፈሉ።
16 አቤቱ፥ የሚፈልጉህ ሁሉ በአንተ ደስ ይበላቸው ሐሤትም ያድርጉ፤ ሁልጊዜ ማዳንህን የሚወድዱ ዘወትር። እግዚአብሔር ታላቅ ይሁን ይበሉ።
17 እኔ ችግረኛና ምስኪን ነኝ፥ ጌታ ግን ያስብልኛል፤ አንተ ረዳቴና መድኃኒቴ ነህ፤ አምላኬ ሆይ፥ አትዘግይ።