ምዕራፍ 81

ለመዘምራን አለቃ፤ በዋሽንት፤ የአሳፍ መዝሙር።

በረድኤታችን በእግዚአብሔር ደስ ይበላችሁ፥ ለያዕቆብም አምላክ እልል በሉ።
2 ዝማሬውን አንሡ ከበሮንም ስጡ፥ ደስ የሚያሰኘውን በገና ከመሰንቆ ጋር፤
3 በመባቻ ቀን በከፍተኛው በዓላችን ቀን መለከትን ንፉ፤
4 ለእስራኤል ሥርዓቱ ነውና፥ የያዕቆብም አምላክ ፍርድ።
5 ከግብጽ በወጣ ጊዜ ለዮሴፍ ምስክር አቆመው። ያላወቅሁትን ቋንቋ ሰማሁ።
6 ጫንቃውን ከሸክም፥ እጆቹንም በቅርጫት ከመገዛት አራቅሁ።
7 በመከራህ ጊዜ ጠራኸኝ አዳንሁህም፥ በተሰወረ ዐውሎም መለስሁልህ፥ በክርክር ውኃ ዘንድም ፈተንሁህ።
8 ሕዝቤ ሆይ፥ስማኝ እነግርሃለሁም፤ እስራኤል ሆይ፥ እመሰክርልሃለሁ።
9 አንተስ ብትሰማኝ ሌላ አምላክ አይሆንልህም፥ ለሌላ አምላክም አትሰግድም።
10 ከግብጽ ምድር ያወጣሁህ እኔ እግዚአብሔር አምላክህ ነኝና፤ አፍህን አስፋ እሞላዋለሁም።
11 ሕዝቤ ግን ቃሌን አልሰሙኝም፥ እስራኤልም አላዳመጠኝም።
12 እንደ ልባቸው ሥራ ተውኋቸው፥ በልባቸውም አሳብ ሄዱ።
13 ሕዝቤስ ሰምቶኝ ቢሆን፥ እስራኤልም በመንገዴ ሄደው ቢሆን፤
14 ጠላቶቻቸውን ፈጥኜ ባዋረድኋቸው ነበር፥ በሚያስጨንቋቸውም ላይ እጄን በጣልሁ ነበር፤
15 የእግዚአብሔር ጠላቶችም በተገዙለት ነበር፥ ዘመናቸውም ለዘላለም በሆነ ነበር፤
16 ከስንዴም ስብ ባበላቸው ነበር፥ ከዓለቱም ማር ባጠገባቸው ነበር።