ምዕራፍ 18

በኢትዮጵያ ወንዞች ማዶ ላለች፥ ክንፍ ያላቸው መርከቦች ላሉባት፥
2 ፤ መልእክተኞችን በባሕር ላይ የደንገል መርከቦችንም በውኃ ላይ ለምትልክ ምድር ወዮላት! እናንተ ፈጣኖች መልእክተኞች ሆይ፥ ወደ ረጅምና ወደ ለስላሳ ሕዝብ፥ ከመጀመሪያው አስደንጋጭ ወደ ሆነ ወገን፥ ወደሚሰፍርና ወደሚረግጥ፥ ወንዞችም ምድራቸውን ወደሚከፍሉት ሕዝብ ሂዱ።
3 ፤ በዓለም የምትኖሩ ሁሉና በምድር የምትቀመጡ ሆይ፥ ምልክት በተራሮች ላይ በተነሣ ጊዜ እዩ፤ መለከትም በተነፋ ጊዜ ስሙ።
4 ፤ እግዚአብሔር። በፀሐይ ጮራ እንደ ደረቅ ትኩሳት፥ በአጨዳም ወራት እንደ ጠል ደመና ሆኜ በማደሪያዬ በጸጥታ ተቀምጬ እመለከታለሁ ብሎኛልና።
5 ፤ እርሱ ከመከር በፊት አበባ በረገፈ ጊዜ የወይንም ፍሬ ጨርቋ ሲይዝ የወይኑን ዘንግ በማጭድ ይቆርጣል፥ ጫፎቹንም ይመለምላል ያስወግድማል።
6 ፤ በተራራ ላይ ላሉ ነጣቂዎች ወፎች፥ ለምድርም አውሬዎች በአንድነት ይቀራሉ፤ ነጣቂዎችም ወፎች ይባጁባቸዋል፥ የምድርም አውሬዎች ሁሉ ይከርሙባቸዋል።
7 ፤ በዚያን ዘመን ለሠራዊት ጌታ ለእግዚአብሔር፥ ከረጅምና ከለስላሳ ሕዝብ፥ ከመጀመሪያው አስደንጋጭ ከሆነ ወገን፥ ከሚሰፍርና ከሚረግጥ፥ ወንዞችም ምድራቸውን ከሚከፍሉት ሕዝብ ዘንድ እጅ መንሻ የሠራዊት ጌታ የእግዚአብሔር ስም ወደሚገኝበት ስፍራ ወደ ጽዮን ተራራ ይቀርባል።