ምዕራፍ 8

በስድስተኛውም ዓመት በስድስተኛው ወር ከወሩም በአምስተኛው ቀን በቤቴ ተቀምጬ ሳለሁ የይሁዳም ሽማግሌዎች በፊቴ ተቀምጠው ሳሉ፥ በዚያ የጌታ የእግዚአብሔር እጅ በላዬ ወደቀች።
2 ፤ እኔም አየሁ፥ እነሆም፥ እንደ እሳት የሚመስል አምሳያ ነበረ፤ ከወገቡም ምሳሌ ወደ ታች እሳት ነበረ፥ ከወገቡም ወደ ላይ እንደ ፀዳል ምሳሌ፥ እንደሚብለጨለጭም የወርቅ ምሳሌ ነበረ።
3 ፤ እጅ መሳይንም ዘረጋ በራስ ጠጕሬም ያዘኝ፤ መንፈስም በምድርና በሰማይ መካከል አነሣኝ፥ በእግዚአብሔርም ራእይ ወደ ኢየሩሳሌም ወደ ሰሜን ወደሚመለከተው ወደ ውስጠኛው አደባባይ በር መግቢያ አመጣኝ፤ በዚያም ቅንዓት የሚያነሣሣ የቅንዓት ጣዖት ተተክሎ ነበር።
4 ፤ እነሆም፥ በቈላው እንዳየሁት ራእይ የእስራኤል አምላክ ክብር በዚያ ነበረ።
5 ፤ እርሱም። የሰው ልጅ ሆይ፥ ዓይንህን ወደ ሰሜን መንገድ አንሣ አለኝ። ዓይኔንም ወደ ሰሜን መንገድ አነሣሁ፤ እነሆም፥ በመሠዊያው በር በሰሜን በኩል በመግቢያው ይህ የቅንዓት ጣዖት ነበረ።
6 ፤ እርሱም። የሰው ልጅ ሆይ፥ የሚያደርጉትን፥ ከመቅደሴ ያርቁኝ ዘንድ የእስራኤል ቤት በዚህ የሚያደርጉትን ታላቁን ርኵሰት ታያለህን? ደግሞም ተመልሰህ ከዚህ የበለጠ ታላቅ ርኵሰት ታያለህ አለኝ።
7 ፤ ወደ አደባባዩም መግቢያ አመጣኝ፤ ባየሁም ጊዜ፥ እነሆ፥ በግንቡ ውስጥ ፉካ ነበረ።
8 ፤ እርሱም። የሰው ልጅ ሆይ፥ ግንቡን ንደለው አለኝ፤ ግንቡንም በነደልሁት ጊዜ መዝጊያ አገኘሁ።
9 ፤ እርሱም። ግባ፥ በዚህም የሚያደርጉትን ክፉውን ርኵሰት እይ አለኝ።
10 ፤ እኔም ገባሁና እነሆ፥ በግንቡ ዙሪያ ላይ የተንቀሳቃሾችና የርኩሳን አራዊት ምሳሌ የእስራኤልንም ቤት ጣዖታት ሁሉ ተስለው አየሁ።
11 ፤ በፊታቸውም ከእስራኤል ቤት ሽማግሌዎች ሰባ ሰዎች ቆመው ነበር፥ በመካከላቸውም የሳፋን ልጅ ያእዛንያ ቆሞ ነበር፥ ሰውም ሁሉ እያንዳንዱ በእጁ ጥናውን ይዞ ነበር፥ የዕጣኑም ጢስ ሽቱ ይወጣ ነበር።
12 ፤ እርሱም። የሰው ልጅ ሆይ፥ የእስራኤል ቤት ሽማግሌዎች በጨለማ እያንዳንዱ በስዕሉ ቤት የሚያደርጉትን አይተሃልን? እነርሱ። እግዚአብሔር አያየንም፤ እግዚአብሔር ምድሪቱን ትቶአታል ይላሉና አለኝ።
13 ፤ እርሱም። ደግሞ ተመልሰህ ከዚህ የበለጠውን የሚያደርጉትን ታላቅ ርኵሰት ታያለህ አለኝ።
14 ፤ ወደ ሰሜንም ወደሚመለከተው ወደ እግዚአብሔር ቤት በር መግቢያ አመጣኝ፤ እነሆም፥ ሴቶች ለተሙዝ እያለቀሱ በዚያ ተቀምጠው ነበር።
15 ፤ እርሱም። የሰው ልጅ ሆይ፥ ይህን አይተሃልን? ደግሞ ተመልሰህ ከዚህ የበለጠ ርኵሰት ታያለህ አለኝ።
16 ፤ ወደ እግዚአብሔር ቤት ወደ ውስጠኛው አደባባይ አመጣኝ፥ እነሆም፥ በእግዚአብሔር መቅደስ መግቢያ ፊት በወለሉና በመሠዊያው መካከል ሀያ አምስት የሚያህሉ ሰዎች ነበሩ ጀርባቸውም ወደ እግዚአብሔር መቅደስ ፊታቸውም ወደ ምሥራቅ ነበረ፤ እነርሱም ወደ ምሥራቅ ለፀሐይ ይሰግዱ ነበር።
17 ፤ እርሱም። የሰው ልጅ ሆይ፥ ይህን አይተሃልን? በዚህ የሚያደርጉትን ይህን ርኵሰት ያደርጉ ዘንድ ለይሁዳ ቤት ጥቂት ነገር ነውን? ምድሪቱን በግፍ ሞልተዋታል ያስቈጡኝም ዘንድ ተመልሰዋል፤ እነሆም፥ ቅርንጫፉን ወደ አፍንጫው አቅርበዋል።
18 ፤ ስለዚህ እኔ ደግሞ በመዓት እሠራለሁ፤ ዓይኔ አይራራም እኔም አላዝንም፤ ወደ ጆሮዬም በታላቅ ድምፅ ቢጮኹ አልሰማቸውም አለኝ።