ምዕራፍ 13

እነሆ፥ ይህን ሁሉ ዓይኔ አየች፤ ጆሮዬም ሰምታ አስተዋለችው።
2 ፤ እናንተ የምታውቁትን እኔ ደግሞ አውቃለሁ፤ ከእናንተ የማንስ አይደለሁም።
3 ፤ ነገር ግን ሁሉን ለሚችል አምላክ መናገር እፈልጋለሁ፥ ከእግዚአብሔርም ጋር ለመዋቀስ እሻለሁ።
4 ፤ እናንተ ግን በሐሰት ለባጮች ናችሁ፤ ሁላችሁ የማትጠቅሙ ባለ መድኃኒቶች ናችሁ።
5 ፤ ምነው ዝም ብላችሁ ብትኖሩ! ይህ ጥበብ በሆነላችሁ ነበር።
6 ፤ አሁንም ክርክሬን ስሙ፥ የከንፈሬንም ሙግት አድምጡ።
7 ፤ በውኑ ስለ እግዚአብሔር ሐሰትን ትናገራላችሁን? ስለ እርሱም ሽንገላን ታወራላችሁን?
8 ፤ ለፊቱስ ታደላላችሁን? ስለ እግዚአብሔርስ ትከራከራላችሁን?
9 ፤ ቢመረምራችሁስ መልካም ይሆንልችኋልን? ወይስ በሰው እንደምትሳለቁ ትሳለቁበታላችሁን?
10 ፤ በስውር ለሰው ፊት ብታደሉ ዘለፋ ይዘልፋችኋል።
11 ፤ ክብሩስ አያስፈራችሁምን? ግርማውስ አይወድቅባችሁምን?
12 ፤ ምስሌዎቻችሁ የአመድ ምሳሌዎች ናቸው፤ ምሽጎቻችሁ የጭቃ ምሽጎች ናቸው።
13 ፤ ዝም በሉ፥ እናገርም ዘንድ ተዉኝ፤ የሆነው ነገር ይምጣብኝ።
14 ፤ ሥጋዬን በጥርሴ እይዛለሁ፥ ሕይወቴንም በእጄ አኖራለሁ።
15 ፤ እነሆ፥ ቢገድለኝ ስንኳ እርሱን በትዕግሥት እጠባበቃለሁ፤ ነገር ግን መንገዴን በፊቱ አጸናለሁ።
16 ፤ ዝንጉ ሰው በፊቱ አይገባምና እርሱ መድኃኒት ይሆንልኛል።
17 ፤ ነገሬን ተግታችሁ ስሙ፥ ምስክርነቴንም በጆሮአችሁ አድምጡ።
18 ፤ እነሆ፥ ሙግቴን አዘጋጅቻለሁ። እንደምጸድቅም አውቃለሁ።
19 ፤ ከእኔስ ጋር የሚፋረድ ማን ነው? አሁን እኔ ዝም ብል እሞታለሁ።
20 ፤ ነገር ግን ሁለት ነገር አታድርግብኝ፤ የዚያን ጊዜ ከፊትህ አልሰወርም፤
21 ፤ እጅህን ከእኔ አርቅ፤ ግርማህም አታስደንግጠኝ።
22 ፤ ከዚያም በኋላ ጥራኝ፥ እኔም እመልስልሃለሁ። ወይም እኔ ልናገር፥ አንተም መልስልኝ።
23 ፤ ያለብኝስ በደልና ኃጢአት ምን ያህል ነው? መተላለፌንና ኃጢአቴን አስታውቀኝ።
24 ፤ ፊትህን ከእኔ የሰወርህ፥ እንደ ጠላትህም የቈጠርኸኝ ስለ ምን ነው?
25 ፤ የረገፈውን ቅጠል ታስጨንቃለህን? ወይስ የደረቀውን ዕብቅ ታሳድዳለህን?
26 ፤ የመረረ ነገር ጽፈህብኛልና፤ የሕፃንነቴንም ኃጢአት ታወርሰኛለህ።
27 ፤ እግሬንም በእግር ግንድ አግብተሃል፥ መንገዴንም ሁሉ መርምረሃል፤ የእግሬን ፍለጋ ወስነሃል።
28 ፤ እኔ እንደሚጠፋ በስባሳ ነገር፥ ብልም እንደሚበላው ልብስ ነኝ።