መጽሐፈ ዜና መዋዕል ቀዳማዊ።

1 2 3 4 5 6 7 8 9 10 11 12 13 14 15 16 17 18 19 20 21 22 23 24 25 26 27 28 29


ምዕራፍ 27

የእስራኤልም ልጆች የአባቶች ቤቶች አለቆችና የሺህ አለቆች የመቶ አለቆችም በክፍሎች ነገር ሁሉ ንጉሡን ያገለገሉትም ሹማምት እንደ ቍጥራቸው እነዚህ ነበሩ። እነዚህም ክፍሎች እያንዳንዳቸው ሀያ አራት ሺህ ሆነው በዓመት ወራት ሁሉ በየወሩ ይገቡና ይወጡ ነበር።
2 ፤ ለመጀመሪያው ወር በአንደኛው ክፍል ላይ የዘብድኤል ልጅ ያሾብዓም ነበረ፤ በእርሱም ክፍል ሀያ አራት ሺህ ጭፍራ ነበረ።
3 ፤ እርሱ ከፋሬስ ልጆች ነበረ፤ ለመጀመሪያው ወር በጭፍራ አለቆች ሁሉ ላይ ተሾሞ ነበር።
4 ፤ በሁለተኛውም ወር ክፍል ላይ አሆሃዊው ዱዲ ነበረ፤ በእርሱም ክፍል ሀያ አራት ሺህ ጭፍራ ነበረ።
5 ፤ ለሦስተኛው ወር ሦስተኛው የጭፍራ አለቃ የካህኑ የዮዳሄ ልጅ በናያስ ነበረ፤ በእርሱም ክፍል ሀያ አራት ሺህ ጭፍራ ነበረ።
6 ፤ ይህ በናያስ በሠላሳው መካከል ኃያል ሆኖ በሠላሳው ላይ ነበረ፤ በእርሱም ክፍል ልጁ ዓሚዛባድ ነበረ።
7 ፤ ለአራተኛው ወር አራተኛው አለቃ የኢዮአብ ወንድም አሣሄል፥ ከእርሱም በኋላ ልጁ ዝባድያ ነበረ፤ በእርሱም ክፍል ሀያ አራት ሺህ ጭፍራ ነበር።
8 ፤ ለአምስተኛው ወር አምስተኛው አለቃ ይዝራዊው ሸምሁት ነበረ፤ በእርሱም ክፍል ሀያ አራት ሺህ ጭፍራ ነበረ።
9 ፤ ለስድስተኛው ወር ስድስተኛው አለቃ የቴቁሐዊው የዒስካ ልጅ ዒራስ ነበረ፤ በእርሱም ክፍል ሀያ አራት ሺህ ጭፍራ ነበረ።
10 ፤ ለሰባተኛው ወር ሰባተኛው አለቃ ከኤፍሬም ልጆች የሆነ ፍሎናዊው ሴሌስ ነበረ፤ በእርሱም ክፍል ሀያ አራት ሺህ ጭፍራ ነበረ።
11 ፤ ለስምንተኛው ወር ስምንተኛው አለቃ ከዛራውያን የነበረው ኩሳታዊው ሲቦካይ ነበረ፤ በእርሱም ክፍል ሀያ አራት ሺህ ጭፍራ ነበረ።
12 ፤ ለዘጠኝኛው ወር ዘጠኝኛው አለቃ ከብንያማውያን የነበረው ዓናቶታዊው አቢዔዜር ነበረ፤ በእርሱም ክፍል ሀያ አራት ሺህ ጭፍራ ነበረ።
13 ፤ ለአሥረኛው ወር አሥረኛው አለቃ ከዛራውያን የነበረው ነጦፋዊው ኖኤሬ ነበረ፤ በእርሱም ክፍል ሀያ አራት ሺህ ጭፍራ ነበረ።
14 ፤ ለአሥራ አንደኛው ወር አሥራ አንደኛው አለቃ ከኤፍሬም ልጆች የነበረው ጲርዓቶናዊው በናያስ ነበረ፤ በእርሱም ክፍል ሀያ አራት ሺህ ጭፍራ ነበረ።
15 ፤ ለአሥራ ሁለተኛው ወር አሥራ ሁለተኛው አለቃ ከጎቶንያል ወገን የነበረው ነጦፋዊው ሔልዳይ ነበረ፤ በእርሱም ክፍል ሀያ አራት ሺህ ጭፍራ ነበረ።
16 ፤ በእስራኤልም ነገዶች ላይ እነዚህ ነበሩ በሮቤላውያን ላይ የዝክሪ ልጅ አልዓዛር አለቃ ነበረ፤ በስምዖናውያን የመዓካ ልጅ ሰፋጥያስ፤
17 ፤ በሌዊ ላይ የቀሙኤል ልጅ ሐሸቢያ፤
18 ፤ በአሮን ላይ ሳዶቅ፤ በይሁዳ ላይ ከዳዊት ወንድሞች ኤሊሁ፤ በይሳኮር ላይ የሚካኤል ልጅ ዖምሪ፤
19 ፤ በዛብሎን ላይ የአብድዩ ልጅ ይሽማያ፤ በንፍታሌም ላይ የዓዝሪኤል ልጅ ኢያሪሙት፤
20 ፤ በኤፍሬም ልጆች ላይ የዓዛዝያ ልጅ ሆሴዕ፤ በምናሴ ነገድ እኵሌታ ላይ የፈዳያ ልጅ ኢዩኤል፤
21 ፤ በገለዓድ ባለው በምናሴ ነገድ እኵሌታ ላይ የዘካርያስ ልጅ አዶ፤ በብንያም ላይ የአበኔር ልጅ የዕሢኤል፤
22 ፤ በዳን ላይ የይሮሐም ልጅ ዓዛርኤል፤ እነዚህ የእስራኤል ልጆች ነገዶች አለቆች ነበሩ።
23 ፤ እግዚአብሔር ግን እስራኤልን እንደ ሰማይ ከዋክብት ያበዛ ዘንድ ተናግሮ ነበርና ዳዊት ከሀያ ዓመት በታች የነበሩትን አልቈጠረም።
24 ፤ የጽሩያ ልጅ ኢዮአብ መቍጠር ጀመረ፥ ነገር ግን አልፈጸመም፤ ስለዚህም በእስራኤል ላይ ቍጣ ሆነ፥ ቍጥራቸውም በንጉሡ በዳዊት መዝገብ አልተጻፈም።
25 ፤ በንጉሡም ቤተ መዛግብት ላይ የዓዲኤል ልጅ ዓዝሞት ሹም ነበረ፤ በሜዳውም በከተሞችም በመንደሮችም በግንቦችም ቤተ መዛግብት ላይ የዖዝያ ልጅ ዮናታን ሹም ነበረ፤
26 ፤ መሬቱን የሚያበጃጁትና እርሻውን በሚያርሱት ላይ የክሉብ ልጅ ዔዝሪ ሹም ነበረ፤
27 ፤ በወይንም ቦታዎች ላይ ራማታዊው ሰሜኢ ሹም ነበረ፤ ለወይንም ጠጅ ዕቃ ቤት በሚሆነው በወይኑ ሰብል ላይ ሸፋማዊው ዘብዲ ሹም ነበረ፤
28 ፤ በቈላውም ውስጥ ባሉት በወይራውና በሾላው ዛፎች ላይ ጌድራዊው በአልሐናን ሹም ነበረ፤ በዘይቱም ቤቶች ላይ ኢዮአስ ሹም ነበረ፤
29 ፤ በሳሮንም በሚሰማሩ ከብቶች ላይ ሳሮናዊው ሰጥራይ ሹም ነበረ፤ በሸለቆቹም ውስጥ በነበሩት ከብቶች ላይ የዓድላይ ልጅ ሻፍጥ ሹም ነበረ፤
30 ፤ በግመሎችም ላይ እስማኤላዊው ኡቢያስ ሹም ነበረ፤ በአህዮቹም ላይ ሜሮኖታዊው ይሕድያ ሹም ነበረ፤
31 ፤ በመንጎቹም ላይ አጋራዊው ያዚዝ ሹም ነበረ። እነዚህ ሁሉ በንጉሡ በዳዊት ሀብት ላይ ሹሞች ነበሩ።
32 ፤ አስተዋይና ጸሐፊ የነበረው የዳዊት አጎት ዮናታን አማካሪ ነበረ፤ የሐክሞኒም ልጅ ይሒኤል ከንጉሡ ልጆች ጋር ነበረ፤
33 ፤ አኪጦፌልም የንጉሡ አማካሪ ነበረ፤ አርካዊውም ኩሲ የንጉሡ ወዳጅ ነበረ፤
34 ፤ ከአኪጦፌልም ቀጥሎ የበናያስ ልጅ ዮዳሄና አብያታር ነበሩ፤ ኢዮአብም የንጉሡ ሠራዊት አለቃ ነበረ።