ምዕራፍ 30

ከእግዚአብሔር ዘንድ ወደ ኤርምያስ የመጣው ቃል ይህ ነው።
2 የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። የነገርሁህን ቃል ሁሉ በመጽሐፍ ጻፍ።
3 እነሆ፥ የሕዝቤን የእስራኤልንና የይሁዳን ምርኮ የምመልስባት ዘመን ይመጣልና፥ ይላል እግዚአብሔር፤ ለአባቶቻቸውም ወደ ሰጠኋት ምድር እመልሳቸዋለሁ፥ እነርሱም ይገዙአታል።
4 እግዚአብሔር ስለ እስራኤልና ስለ ይሁዳ የተናገረው ቃል ይህ ነው።
5 እግዚአብሔር እንዲህ ይላልና። የሚያስፈራ ድምፅ ሰምተናል፤ የፍርሃት ነው እንጂ የሰላም አይደለም።
6 ጠይቁ፥ ወንድ ይወልድ እንደ ሆነ ተመልከቱ፤ ስለ ምን ሰው ሁሉ እንደ ወላድ እጁን በወገቡ ላይ አድርጎ ፊቱም ሁሉ ወደ ጥቁረት ተለውጦ አየሁ?
7 ወዮ! ያ ቀን ታላቅ ነውና፥ እርሱንም የሚመስል የለምና፤ ያ የያዕቆብ መከራ ዘመን ነው፥ ነገር ግን ከእርሱ ይድናል።
8 በዚያ ቀን እንዲህ ይሆናል፥ ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፤ ቀንበርን ከአንገትህ እሰብራለሁ፥ እስራትህንም እበጥሳለሁ፥ ከእንግዲህ ወዲህም ለሌላ አትገዛም፤
9 ለአምላካቸው ለእግዚአብሔርም ለማስነሣላቸው ለንጉሣቸው ለዳዊትም ይገዛሉ እንጂ ሌሎች አሕዛብ እንደ ገና አይገዙአቸውም።
10 እነሆ፥ አንተን ከሩቅ ዘርህንም ከምርኮ አገር አድናለሁና ባሪያዬ ያዕቆብ ሆይ፥ አትፍራ፥ ይላል እግዚአብሔር፥ አንተም እስራኤል ሆይ፥ አትደንግጥ፤ ያዕቆብም ይመለሳል ያርፍማል ተዘልሎም ይቀመጣል፤ ማንም አያስፈራውም።
11 አድንህ ዘንድ ከአንተ ጋር ነኝና፥ ይላል እግዚአብሔር፤ አንተንም የበተንሁባቸውን አሕዛብን ሁሉ ፈጽሜ አጠፋለሁ፥ አንተን ግን ፈጽሜ አላጠፋህም፤ በመጠን እቀጣሃለሁ፥ ያለ ቅጣትም ከቶ አልተውህም።
12 እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። ስብራትህ የማይፈወስ ቍስልህም ክፉ ነው።
13 ትጠገን ዘንድ ክርክርህን የሚፈርድልህ የለም፥ ቍስልህንም የሚፈውስ መድኃኒት የለህም።
14 ውሽሞችህ ሁሉ ረስተውሃል አይፈልጉህምም፤ በደልህ ታላቅ ስለሆነ ኃጢአትህም ስለ በዛ፥ በጠላት ማቍሰልና በጨካኝ ቅጣት አቍስዬሃለሁና።
15 ሕመምህ የማይፈወስ ሆኖአልና ስለ ስብራትህ ለምን ትጮኻለህ? በደልህ ታላቅ ስለሆነ ኃጢአትህም ስለ በዛ፥ ይህን አድርጌብሃለሁ።
16 ስለዚህ የሚውጡህ ሁሉ ይዋጣሉ፥ ጠላቶችህም ሁላቸው ይማረካሉ፤ የዘረፉህም ይዘረፋሉ፥ የበዘበዙህንም ሁሉ ለመበዝበዝ አሳልፌ እሰጣለሁ።
17 እኔ ጤናህን እመልስልሃለሁ ቍስልህንም እፈውሳለሁ፥ ይላል እግዚአብሔር፤ ማንም የማይሻት፥ የተጣለች ጽዮን ብለው ጠርተውሻልና።
18 እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። እነሆ፥ የያዕቆብን ድንኳን ምርኮ እመልሳለሁ፥ ለማደሪያውም እራራለሁ፤ ከተማይቱም በጉብታዋ ላይ ትሠራለች፥ አዳራሹም እንደ ዱሮው የሰው መኖሪያ ይሆናል።
19 ከእርሱም ዘንድ የምስጋናና የዘፋኞች ድምፅ ይወጣል፤ እኔም አበዛቸዋለሁ አያንሱምም፥ እኔም አከብራቸዋለሁ ታናሽም አይሆኑም።
20 ልጆቻቸውም እንደ ቀድሞ ይሆናሉ፥ ማኅበራቸውም በፊቴ ጸንቶ ይኖራል፤ የሚያስጨንቋቸውንም ሁሉ እቀጣለሁ።
21 አለቃቸው ከእነርሱ ውስጥ ይሆናል፥ ገዥአቸውም ከመካከላቸው ይወጣል፤ እኔ አቀርበዋለሁ እርሱም ይቀርባል፤ ይህስ ባይሆን ወደ እኔ ለመቅረብ የሚደፍር ማን ነው? ይላል እግዚአብሔር።
22 እናንተም ሕዝብ ትሆኑኛላችሁ እኔም አምላክ እሆናችኋለሁ።
23 እነሆ፥ የእግዚአብሔር ዐውሎ ነፋስ፥ እርሱም ቍጣው፥ የሚያገለባብጥ ዐውሎ ነፋስ ወጥቶአል፤ የዓመፀኞችንም ራስ ይገለባብጣል።
24 የእግዚአብሔር ጽኑ ቍጣ የልቡን አሳብ ሠርቶ እስኪፈጽም ድረስ አይመለስም በኋለኛው ዘመን ታስተውሉታላችሁ።