ምዕራፍ 21

ዳዊትም ወደ ካህኑ ወደ አቢሜሌክ ወደ ኖብ መጣ፤ አቢሜሌክም እየተንቀጠቀጠ ዳዊትን ሊገናኘው መጣና። ስለ ምን አንተ ብቻህን ነህ? ከአንተስ ጋር ስለ ምን ማንም የለም? አለው።
2 ፤ ዳዊትም ካህኑን አቢሜሌክን። የተላክህበትን ነገርና የሰጠሁህን ትእዛዝ ማንም አይወቅ ብሎ ንጉሡ አንድ ነገር አዝዞኛል፤ ስለዚህም ብላቴኖቹን እንዲህ ባለ ስፍራ ተውኋቸው።
3 ፤ አሁንስ በእጅህ ምን አለ? አምስት እንጀራ ወይም የተገኘውን በእጄ ስጠኝ አለው።
4 ፤ ካህኑም ለዳዊት መልሶ። ሁሉ የሚበላው እንጀራ የለኝም፥ ነገር ግን የተቀደስ እንጀራ አለ፤ ብላቴኖቹ ከሴቶቹ ንጹሐን እንደ ሆኑ መብላት ይቻላል አለው።
5 ፤ ዳዊትም ለካህኑ መልሶ። በእውነት ከወጣን ጀምረን እኛ ሰውነታችንን ከሴቶች ሦስት ቀን ጠብቀናል፤ የብላቴኖችም ዕቃ የተቀደሰች ናት፤ ስለዚህ ዛሬ ዕቃቸው የተቀደሰች በመሆንዋ እንጀራው እንደሚበላ እንጀራ ይሆናል አለው።
6 ፤ ካህኑም በእርሱ ፋንታ ትኩስ እንጀራ ይደረግ ዘንድ ከእግዚአብሔር ፊት ከተነሣው ከገጹ ኅብስት በቀር ሌላ እንጀራ አልነበረምና የተቀደሰውን እንጀራ ሰጠው።
7 ፤ በዚያም ቀን ከሳኦል ባሪያዎች አንድ ሰው በዚያ በእግዚአብሔር ፊት ተገኝቶ ነበር፤ ስሙም ኤዶማዊው ዶይቅ ነበረ፥ ለሳኦልም የእረኞቹ አለቃ ነበረ።
8 ፤ ዳዊትም አቢሜሌክን። የንጉሥ ጉዳይ ስላስቸኰለኝ ሰይፌንና መሣሪያዬን አላመጣሁምና በአንተ ዘንድ ጦር ወይም ሰይፍ አለ ወይ? አለው።
9 ፤ ካህኑም። በኤላ ሸለቆ የገደልኸው የፍልስጥኤማዊው የጎልያድ ሰይፍ፥ እነሆ፥ በመጎናጸፊያ ተጠቅልሎ ከዚህ ከኤፉዱ በኋላ አለ፤ ትወድደውም እንደ ሆነ ውሰደው፤ ሌላ ከዚህ የለም አለ። ዳዊትም። እንደ እርሱ ያለ የለምና እርሱን ስጠኝ አለው።
10 ፤ ዳዊትም ተነሣ በዚያም ቀን ሳኦልን ፈርቶ ሸሸ፥ ወደ ጌትም ንጉሥ ወደ አንኩስ ሄደ።
11 ፤ የአንኩስ ባሪያዎችም። ይህ ዳዊት የአገሩ ንጉሥ አይደለምን? ሳኦል ሺህ፥ ዳዊትም እልፍ ገደለ ብለው ሴቶች በዘፈን የዘመሩለት እርሱ አይደለምን? አሉት።
12 ፤ ዳዊትም ይህን ቃል በልቡ አኖረ፥ የጌትንም ንጉሥ አንኩስን እጅግ ፈራ።
13 ፤ በፊታቸውም አእምሮውን ለወጠ፥ በያዙትም ጊዜ እንደ እብድ ሆነ፥ በበሩም መድረክ ላይ ተንፈራፈረ፥ ልጋጉም በጢሙ ላይ ይወርድ ነበር።
14 ፤ አንኩስም ባሪያዎቹን። እነሆ፥ ይህ ሰው እብድ እንደ ሆነ አይታችኋል፤ ለምን ወደ እኔ አመጣችሁት? በፊቴ ያብድ ዘንድ ይህን ያመጣችሁት እብድ ጠፍቶብኝ ነውን? እንዲህ ያለውስ ወደ ቤቴ ይገባልን? አላቸው።
15