ምዕራፍ 6

ልጄ ሆይ፥ ለጎረቤትህ ዋስ ብትሆን፥ ስለ ሌላ ሰው እጅህን አጋና ብትመታ፥
2 በአፍህ ቃል ተጠመድህ፤ በአፍህ ቃል ተያዝህ።
3 ልጄ ሆይ፥ ይህን አድርግ ራስህንም አድን፥ በጎረቤትህ እጅ ወድቀሃልና፤ ፈጥነህ ሂድ፥ ጎረቤትህንም ነዝንዘው።
4 ለዓይንህ እንቅልፍን ለሽፋሽፍቶችህም እንጕልቻን አትስጥ፥
5 እንደ ሚዳቋ ከአዳኝ እጅ፥ እንደ ወፍም ከአጥማጅ እጅ ትድን ዘንድ።
6 አንተ ታካች፥ ወደ ገብረ ጕንዳን ሂድ፥ መንገድዋንም ተመልክተህ ጠቢብ ሁን።
7 አለቃና አዛዥ ገዢም ሳይኖራት
8 መብልዋን በበጋ ታሰናዳለች፥ መኖዋንም በመከር ትሰበስባለች።
9 አንተ ታካች፥ እስከ መቼ ትተኛለህ? ከእንቅልፍህስ መቼ ትነሣለህ?
10 ጥቂት ትተኛለህ፥ ጥቂት ታንቀላፋለህ፥ ትተኛም ዘንድ ጥቂት እጅህን ታጥፋለህ፤
11 እንግዲህ ድህነትህ እንደ ወንበዴ፥ ችጋርህም ሰይፍ እንደ ታጠቀ ሰው ይመጣብሃል።
12 ምናምንቴ ሰው የበደለኛም ልጅ በጠማማ አፍ ይሄዳል፤
13 በዓይኑ ይጠቅሳል፥ በእግሩ ይናገራል፥ በጣቱ ያስተምራል፤
14 ጠማማነት በልቡ አለ፥ ሁልጊዜም ክፋትን ያስባል፤ ጠብንም ይዘራል።
15 ስለዚህ ጥፋቱ ድንገት ይደርስበታል፤ ድንገት ይደቅቃል፥ ፈውስም ከቶ የለውም።
16 እግዚአብሔር የሚጠላቸው ስድስት ነገሮች ናቸው፥ ሰባትንም ነፍሱ አጥብቃ ትጸየፈዋለች፤
17 ትዕቢተኛ ዓይን፥ ሐሰተኛ ምላስ፥ ንጹሕን ደም የምታፈስስ እጅ፥
18 ክፉ አሳብን የሚያበቅል ልብ፥ ወደ ክፉ የምትሮጥ እግር፥
19 በሐሰት የሚናገር ሐሰተኛ ምስክር በወንድማማች መካከልም ጠብን የሚዘራ።
20 ልጄ ሆይ፥ የአባትህን ትእዛዝ ጠብቅ፥ የእናትህንም ሕግ አትተው፤
21 ሁልጊዜም በልብህ አኑረው፥ በአንገትህም እሰረው።
22 ስትሄድም ይመራሃል፤ ስትተኛ ይጠብቅሃል፤ ስትነሣ ያነጋግርሃል።
23 ትእዛዝ መብራት፥ ሕግም ብርሃን ነውና፥ የተግሣጽም ዘለፋ የሕይወት መንገድ ነውና፥
24 ከክፉ ሴት ትጠብቅህ ዘንድ፥ ከሌላይቱም ሴት ምላስ ጥፍጥነት።
25 ውበትዋን በልብህ አትመኘው፤ ሽፋሽፍትዋም አያጥምድህ።
26 የጋለሞታ ዋጋ እስከ አንዲት እንጀራ ነው፤ አመንዝራም ሴት የሰውን ሕይወት ታጠምዳለች።
27 በጉያው እሳትን የሚታቀፍ፥ ልብሶቹስ የማይቃጠሉ ማን ነው?
28 በፍም ላይ የሚሄድ እግሮቹስ የማይቃጠሉ ማን ነው?
29 ወደ ሰው ሚስት የሚገባም እንዲሁ ነው፤ የሚነካትም ሁሉ ሳይቀጣ አይቀርም።
30 ሌባ በተራበ ጊዜ ነፍሱን ሊያጠግብ ቢሰርቅ ሰዎች አይንቁትም፤
31 ቢያዝም ሰባት እጥፍ ይከፍላል፥ በቤቱም ያለውን ሁሉ ይሰጣል።
32 ከሴት ጋር የሚያመነዝር ግን አእምሮው የጐደለ ነው፤ እንዲሁም የሚያደርግ ነፍሱን ያጠፋል።
33 ቍስልንና ውርደትን ያገኛል፥ ስድቡም አይደመሰስም።
34 ቅንዓት ለሰው የቍጣ ትኵሳት ነውና፥ በበቀል ቀን አይራራለትምና።
35 እርሱም ምንም ካሣ አይቀበልም፥ ስጦታም ብታበዛለት አይታረቅም።