ምዕራፍ 25

አሜስያስም መንገሥ በጀመረ ጊዜ የሀያ አምስት ዓመት ጕልማሳ ነበረ፥ በኢየሩሳሌምም ሀያ ዘጠኝ ዓመት ነገሠ፤ እናቱ ዮዓዳን የተባለች የኢየሩሳሌም ሴት ነበረች።
2 ፤ በእግዚአብሔርም ፊት ቅን ነገር አደረገ፥ ነገር ግን በፍጹም ልብ አይደለም።
3 ፤ መንግሥትም በጸናለት ጊዜ አባቱን የገደሉትን ባሪያዎች ገደለ።
4 ፤ በሙሴም ሕግ መጽሐፍ እንደ ተጻፈ፥ እግዚአብሔርም። ሰው ሁሉ በገዛ ኃጢያቱ ይሙት እንጂ አባቶች በልጆች ፋንታ አይሙቱ፥ ልጆችም በአባቶች ፋንታ አይሙቱ ብሎ እንዳዘዘ የነፍሰ ገዳዮችን ልጆች አልገደለም።
5 ፤ አሜስያስም ይሁዳን ሰበሰበ፥ በእየአባቶቻቸውም ቤቶች ከሺህ አለቆችና ከመቶ አለቆች እጅ በታች አቆማቸው፤ ከሀያ ዓመት ጀመሮ ከዚያም በላይ ያሉትን ይሁዳንና ብንያምን ሁሉ ቈጠረ፥ ለሰልፍም የሚወጡ፥ ጋሻና ጦርም የሚይዙ ሦስት መቶ ሺህ የተመረጡ ሰዎች አገኘ።
6 ፤ ደግሞም ከእስራኤል ዘንድ መቶ ሺህ ጽኑዓን ኃያላን በመቶ መክሊት ብር ቀጠረ።
7 ፤ አንድ የእግዚአብሔር ሰው ግን ወደ እርሱ መጥቶ። ንጉሥ ሆይ፥ እግዚአብሔር ከእስራኤልና ከኤፍሬም ልጆች ጋር አይደለምና የእስራኤል ጭፍራ ከአንተ ጋር አይውጣ።
8 ፤ ብትሄድ ግን፥ በእነርሱም ማሸነፍን ብታስብ፥ የመርዳትና የመጣል ኃይል ከእግዚአብሔር ዘንድ ነውና እግዚአብሔር በጠላቶችህ ፊት ይጥልሃል አለው።
9 ፤ አሜስያስም የእግዚአብሔርን ሰው። ለእስራኤል ጭፍራ የሰጠሁት መቶ መክሊት ምን ይሁን? አለው። የእግዚአብሔርም ሰው። ከዚህ አብልጦ ይሰጥህ ዘንድ እግዚአብሔር ይችላል ብሎ መለሰለት።
10 ፤ አሜስያስም ከኤፍሬም የመጡት ጭፍሮች ወደ ስፍራቸው ይመለሱ ዘንድ ለይቶ አሰናበታቸው፤ ስለዚህም ቍጣቸው በይሁዳ ላይ ጸና፥ ወደ አገራቸውም በጽኑ ቍጣ ተመለሱ።
11 ፤ አሜስያስም በረታ፥ ሕዝቡንም አውጥቶ ወደ ጨው ሸለቆ ሄደ፥ ከሴይርም ልጆች አሥር ሺህ ገደለ።
12 ፤ የይሁዳም ልጆች ደግሞ አሥር ሺህ ሰዎችን በሕይወታቸው ማረኩ፥ ወደ ዓለቱም ራስ ላይ አመጡአቸው፤ ከዓለቱም ራስ ላይ ጣሉአቸው፥ ሁሉም ተፈጠፈጡ።
13 ፤ አሜስያስ ግን ከእርሱ ጋር ወደ ሰልፍ እንዳይሄዱ ያሰናበታቸው ጭፍሮች ከሰማርያ ጀምረው እስከ ቤትሖሮን ድረስ በይሁዳ ከተሞች ላይ አደጋ ጣሉ፥ ከእነርሱም ሦስት ሺህ ገደሉ፥ ብዙ ምርኮም ማረኩ።
14 ፤ አሜስያስም የኤዶምያስን ሰዎች ከገደለ በኋላ የሴይርን ልጆች አማልክት አመጣ፥ የእርሱም አማልክት ይሆኑ ዘንድ አቆማቸው፥ ይሰግድላቸውም ያጥንላቸውም ነበር።
15 ፤ ስለዚህም የእግዚአብሔር ቍጣ በአሜስያስ ላይ ነደደና። ሕዝባቸውን ከአንተ እጅ ያላዳኑትን የአሕዛብን አማልክት ስለ ምን ፈለግሃቸው? የሚል ነቢይ ሰደደበት።
16 ፤ እርሱም ሲናገር ንጉሡ። በውኑ አንተ የንጉሡ አማካሪ ልትሆን ሾመነሃልን? ተው፤ ቅጣትን ስለ ምን ትሻለህ? አለው። ነቢዩም። ይህን አድርገሃልና፥ ምክሬንም አልሰማህምና እግዚአብሔር ሊያጠፋህ እንዳሰበ አወቅሁ ብሎ ተወ።
17 ፤ የይሁዳም ንጉሥ አሜስያስ ምክር አደረገና። ና፥ እርስ በርሳችን ፊት ለፊት እንተያይ ብሎ ወደ እስራኤል ንጉሥ ወደ ኢዩ ልጅ ወደ ኢዮአካዝ ልጅ ወደ ኢዮአስ ላከ።
18 ፤ የእስራኤልም ንጉሥ ኢዮስያስ። የሊባኖስ ኵርንችት። ልጅህን ለልጄ ሚስት አድርገህ ስጠው ብሎ ወድ ሊባኖስ ዝግባ ላከ፤ የሊባኖስም አውሬ አልፎ ኵርንችቱን ረገጠ።
19 ፤ አንተም። እነሆ፥ ኤዶምያስን መትቻለሁ ብለህ ኰርተሃል፤ በቤትህ ተቀመጥ፤ አንተ ከይሁዳ ጋር ትወድቅ ዘንድ ስለ ምን መከራ ትሻላህ? ብሎ ወደ ይሁዳ ንጉሥ ወደ አሜስያስ ላከ።
20 ፤ የኤዶምያስንም አማልክት ስለ ፈለጉ በጠላቶቻቸው እጅ አሳልፎ ይሰጣቸው ዘንድ የእግዚአብሔር ፈቃድ ነበረና አሜስያስ አልሰማም።
21 ፤ የእስራኤልም ንጉሥ ኢዮአስ ወጣ፤ እርሱና የይሁዳ ንጉሥ አሜስያስም በይሁዳ ባለች በቤትሳሚስ ላይ እርስ በርሳቸው ተያዩ።
22 ፤ ይሁዳም በእስራኤል ፊት ተመታ፥ እያንዳንዱም ወደ ድንኳኑ ሸሸ።
23 ፤ የእስራኤልም ንጉሥ ኢዮአስ የይሁዳን ንጉሥ የአካዝያስን ልጅ የኢዮአስን ልጅ አሜስያስን በቤትሳሚስ ይዞ ወደ ኢየሩሳሌም አመጣው፥ የኢየሩሳሌምንም ቅጥር ከኤፍሬም በር ጀምሮ እስከ ማዕዘኑ በር ድረስ አራት መቶ ክንድ አፈረሰ።
24 ፤ ወርቁንና ብሩን ሁሉ፥ በእግዚአብሔርም ቤት ከዖቤድኤዶም ጋር የነበሩትን ዕቃዎች ሁሉ፥ የንጉሡን ቤት መዛግብት፥ በመያዣ የተያዙትንም ወስዶ ወደ ሰማርያ ተመለሰ።
25 ፤ የይሁዳም ንጉሥ የኢዮአስ ልጅ አሜስያስ ከእስራኤል ንጉሥ ከኢዮአካዝ ልጅ ከኢዮአስ ሞት በኋላ አሥራ አምስት ዓመት ኖረ።
26 ፤ የቀረውም የፊተኛውና የኋላኛው የአሜስያስ ነገር፥ እነሆ፥ በይሁዳና በእስራኤል ነገሥታት መጽሐፍ የተጻፈ አይደለምን?
27 ፤ አሜስያስም እግዚአብሔርን ከመከተል ከራቀ በኋላ በኢየሩሳሌም የዓመፅ መሐላ አደረጉበት፥ ወደ ለኪሶም ኰበለለ፤ በስተ ኋላውም ወደ ለኪሶ ላኩ፥ በዚያም ገደሉት።
28 ፤ በፈረስም ጭነው አመጡት፥ በዳዊትም ከተማ ከአባቶቹ ጋር ቀበሩት።